Tuesday, 2 February 2016

PART 6 አንድ ጥያቄና አስር መልሶቹ!

    አንድ ጥያቄና አስር መልሶቹ!

በመጨረሻም ከላይኛው ጥያቄ ጋር ተያይዞ የሚነሳ አንድ የተለመደ መፈክር አለ፦ «አላህ ዐርሽ ወይም ሌላ ቦታ አያስፈልገውም!»
ይህን አስመልክቶ ሁለት መልሶችን ብቻ እንጥቀስ፦
‪#‎1ኛ፦ አላህ ከዐርሹ በላይ የሆነው ቦታ ስለሚያስፈልገው እንደሆነ የሞገተ አንድም ሙስሊም ሳይኖር ይህንን ክርክር ማንሳት ከንቱ ነው፤ ከርዕሱ የወጣም ዛዛታ ነው!
አላህ ከማንኛውም ፍጡር ምንም አይነት እርዳታ የማይፈልግ ተብቃቂ ጌታ ነው! ዐርሽን፣ ሰማያትንና ምድርን እንዲሁም መላ ፍጡራንን በወሰን-የለሽ ችሎታው የሚቆጣጠረውና የሚያስተናብረው ማን ሆነና?! ያለ እርሱ እርዳታ የትኛውም ፍጡር ሊኖርም ሆነ ሊቆም መች ይችልና?! ሃያሉ አምላካችን ልቅናና ጥራት የተገባው ነው!
إِنَّ ٱللَّهَ يُمۡسِكُ ٱلسَّمَٰوَٰتِ وَٱلۡأَرۡضَ أَن تَزُولَاۚ وَلَئِن زَالَتَآ إِنۡ أَمۡسَكَهُمَا مِنۡ أَحَدٖ مِّنۢ بَعۡدِهِۦٓۚ إِنَّهُۥ كَانَ حَلِيمًا غَفُورٗا
= «አላህ ሰማያትንና ምድርን እንዳይወገዱ ይይዛቸዋል፤ ቢወገዱ ከርሱ ሌላ አንድም የሚይዛቸው የለም! እነሆ እርሱ ሁሌም ታጋሽ መሀሪ ነውና።» [ፋጢር 41]
ግን ይህ የሚያሳየው ጀህሚያዎችና ተከታዮቻቸው በቁርኣንና በሱን-ናህ የተረጋገጡትን የጌታ ባህሪያት መልዕክት እንዲቆለምሙ ያደረጋቸው ቀድሞውኑ የመረጃዎቹን መልዕክት የተረዱት የፍጡራን ባህሪያትን በሚረዱበት ይዘት መሆኑን ነው!
ለምሳሌ፦ አላህ በዐርሹ ላይ መሆኑን የሚያረጋግጡ ማስረጃዎችን ሲሰሙ የሚገነዘቡት መልዕክት አንድ ፍጡር በሌላ ነገር ላይ መሆኑን በሚገነዘቡበት ይዘት ስለሆነ “አላህ ከዐርሽ በላይ ከሆነ ለርሱ ዐርሽ ያስፈልገዋል ማለት ነው! ዐርሽ ይሸከመዋል ማለት ነው! ..ወዘተ” በሚል ፈሊጥ የበላይነት መገለጫውን ወደማፋረስ አቀኑ! አዎን! እነርሱ ናቸው አመሳሳዮቹ! ቀድሞውኑ ይህን የፍጡር መገለጫ ከማስረጃዎቹ የሚረዳው ህሊናው በማመሳሰል አባዜ የተበከለ ብቻ ነውና!
ይህንና ሌሎች ትክክለኛ መገለጫዎቹን ያለ ምንም አጉል ፈሊጥ ለጌታ ማንነት በሚገባው መልኩ የሚያፀድቁት ሌሎች ሙስሊሞች ግን አላህ ከእንደዚህ አይነት ጉድለት የጠራ መሆኑን አስቀድመው ስለሚያምኑ መረጃዎቹን ማጣመም አላስፈለጋቸውም!

‪#‎2ኛ- አላህ በጥበቡ የሚፈፅማቸውን አድራጎቶች በእንዲህ ያለ ሰንካላ መነሻ መጋፈጥ አያስኬድም!
አላህ ማንኛውንም ነገር በአንድ ቃል በቅፅበት ማከናወን የሚችል ሃያል ጌታ ከመሆኑ ጋር በጥበቡ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀናት ፈጥሯል። ታዲያ እርሱ ምንም የሚሳነው ባለመሆኑ ብቻ የስድስት ቀናቱን እውነታ እናስተባብላለን?!
እንዲሁም አላህ የማንም እገዛ ሳያስፈልገው ሁሉን ማከናወን የሚችል ከመሆኑ ጋር የተለያዩ የፍጥረተ አለም ክንውኖችን በርሱ ፈቃድ የሚያስተናብሩ መላእክትን ፈጥሯል። ታዲያ እርሱ እገዛ የሚያስፈልገው ባለመሆኑ የመላኢካን ህልውና እንክዳለን?!
ለእንዲህ አይነት ጥያቄ በር ከተከፈተ በአንፃሩ ደግሞ ማብቂያ የሌላቸው ምሳሌዎችም ይዥጎደጎዳሉ!
ያሳለፍናቸውን ነጥቦች በአጭሩ እንከልሳቸው፦
*ጥቅል ምላሾቹ አምስት ሲሆኑ እነርሱም እንደሚከተለው ይቀርባሉ፦
1- የአላህ ከበላይነት በፅኑ ማስረጃዎች የተረጋገጠ በመሆኑ ጥያቄን አያስተናግድም!
2- በአንፃሩ ደግሞ ይህ ሙግት በየትኛውም መረጃ ላይ አይገኝም!
3- መሰል ጥያቄዎችን ማንሳት የተወገዘ ፈጠራ ነው!
4- ተውሒድ በንፅፅራዊ አመክንዮ አይለካም!
5- ያላወቅነው እውነታ ያወቅነውን አይሽርም!
*ዝርዝር ምላሾቹ ደግሞ ባጭሩ የሚከተሉት ነበሩ፦
1- «ቅድሚያ የት ነበር?!» የሚለው ቃና ራሱ ስህተት ነው! ምንም ባልነበረበት ከምን በላይ ነበር ይባላል?!
2- «ዐርሽም ሆነ ሌላ ቦታ ሳይፈጠር የነበረ ጌታ ነው!..» የሚለው ደግሞ ከዐርሹ በላይ ከመሆኑ ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ አይጋጭም!
3- «..የማይቀያየር ጌታ ስለሆነ..» የሚለው ደግሞ የማሸማቀቂያ ስልት እንደሆነና ከዐርሹ በላይ መሆኑ በየትኛውም ቋንቋ "መቀየር" ተብሎ እንደማይጠራ፣ ያንንም የሚያስገነዝብ እንዳልሆነ ተብራርቷል።
4- «አሁንም እንደያኔው ያለ ቦታ ነው..» የሚለው አሻሚ ቃል ደግሞ "ቦታ" የፍጡራን ክልል ውስጥ ያለ ግኝ ስፍራ ከታሰበበት ያስማማናል፤ ከቦታዎች ክልል ውጭ ያለው በአንፃራዊ ገለፃ "ቦታ" ከተሰኘ ደግሞ ቃሉን ፈርተን የበላይነቱን አናስተባብልም!
5- የአላህ ህልውና እውን መሆኑን ካመኑ ፍጡራኑን ያስገኘው ከራሱ ውጭ ነውና ሁሌም ከበላያቸው እንጂ ከበታች እንደማይሆን ሊያረጋግጡ የግድ ይላል!
*በመጨረሻም "አላህ ቦታ አያስፈልገውም!" የሚለው ነጥብ ውዝግብ የሌለበት መሆኑንና በዐርሹ ላይ መሆኑ መገለፁም ይህንን ጉድለት የሚያስገነዝብ እንዳልሆነ በምሳሌዎች ቃኝተናል!
ለጊዜው ጨርሻለሁ!
@ በሸይኽ ኢልያስ አህመድ

PART 5 አንድ ጥያቄና አስር መልሶቹ!

    አንድ ጥያቄና አስር መልሶቹ!

(2-4) «..አላህ አሁንም ያለ ቦታ ነው!» የሚለው ገለፃ ደግሞ በሚከተሉት ነጥቦች ይብራራል፦
“ቦታ” የሚለው ቃል ሁለት አይነት ግንዛቤን ሊያስጨብጥ የሚችል በመሆኑ የተፈለገበትን መልዕክት ሳናጣራ በደፈናው ማፅደቅ ወይም ማፋረስ ተገቢ አይሆንም። ስለዚህም፦
1- “ቦታ” በፍጥረታት ክልል የተገደበ ግኝ ስፍራ ከታሰበበት በርግጥ አላህ ከፍጥረተ አለሙ ውጭ ነውና በእንዲህ ያለ “ቦታ” አይደለም!
ዐርሽ የፍጥረት ክልል ማብቂያ የመጨረሻው ጣሪያ ነውና! አላህ ከዐርሹ በላይ መሆኑን መናገር ደግሞ ይህንን አያስገነዝብም! በተለያዩ ቁርኣናዊና ነብያዊ ማስረጃዎች ላይ “በሰማይ” መሆኑ መነገሩ ደግሞ ስርወቃሉ በዐረብኛ ቋንቋ ጥቅል ከፍታን የሚጠቁም በመሆኑ እንጂ አላህ እንደ መላእክት በሰማያት ውስጥ የተገደበ እንደሆነ የሚያስብ አንድም ሙስሊም የለም!
2- ከቦታዎች ወሰን ውጭና ከፍጥረታት ክልል በላይ ያለው በአንፃራዊ ይዘቱ እንደ “ቦታ” ከታሰበ ደግሞ ቃሉን ፈርተን ብቻ ስፍር ቁጥር በሌላቸው መረጃዎች የተረጋገጠውን የበላይነቱን አናስተባብልም።

 በየትኛውም የአላህ፣ የመልዕክተኛውና የቀደምት ምርጥ ትውልዶች ንግግር ላይ ጭራሽ ባልተወሳው “አላሁ መውጁዱን ቢላ መካን!” (አላህ ያለ ቦታ ያለ ነው!) በሚለው የኑፋቄ መፈክር ተሸብረን እንዲህ ቁልጭ ያለ ሸሪዓዊና አእምሯዊ እውነታን አንጋፋም!
- እንዲያውም ስለ አላህ ከሁሉም ፍጡር ይበልጥ አዋቂ የሆኑት መልዕክተኛ የባሪያዪቱን አማኝነት ለማረጋገጥ “አላህ የት ነው?” ማለታቸው ይህን እውነታ አጉልቶ ያሳያል! [ሰሒሑ ሙስሊም ቁጥር (537) ይመልከቱ!]
በዚሁ አጋጣሚ “አላህ ያለ ቦታ ነው!” የሚለው መፈክር ከሙዕተዚላዎች የተወረሰ መሆኑን ለማረጋገጥ ከፈለጉ መቃላቱ’ል-ኢስላሚይ-ዪን” የተሰኘውን የአቡ’ል-ሐሰን አል-አሽዐሪይ መፅሐፍ ጥራዝ 1 ገፅ 286 ይመልከቱ!
- «አላህ በሁለተኛው መልእክት ላይ በተብራራው "ቦታ" ላይም አይደለም!» ካሉ ደግሞ ህልውናውን እያፋረሱ ነው!
የሚከተለው ነጥብ ይህን ይበልጥ ያጎላል፦

(2-5) ህልውና ወይስ ህሊናዊ?!

ልብ ይበሉ! የጥያቄው ውጤት የሚያመራው የፈጣሪን የበላይነት ወደ ማረጋገጥ እንጂ ወደ ማስተባበል ሊሆን አይችልም!
ለዚህም አል-ኢማም አሕመድ (241 ዓ.ሂ) በፅሁፋቸው ያሰፈሩትን የሚከተለውን አእምሯዊ እውነታ እናስተውል፦

قال الإمام أحمد ابن حنبل: وإذا أردت أن تعلم أن الجهميّ كاذبٌ على الله حين زعم أن الله في كل مكان، ولا يكون في مكان دون مكان، فقل له: أليس الله كان ولا شيء؟ فسيقول: نعم. فقل له: حين خلَقَ الشيءَ خلقَه في نفسه أو خارجًا من نفسه؟ فإنه يصير إلى ثلاثة أقاويل، لابد له من واحد منها:
إن زعم أن الله خَلَق الخلْق في نفسه فقد كفر، حين زعم أنه خلق الجن والشياطين وإبليس في نفسه.
إن قال: خلقهم خارجًا من نفسه ثم دخل فيهم، كان هذا كفرًا أيضًا حين زعم أنه دخل في كل مكان وحشٍ قذِر رديء.
وإن قال: خلقهم خارجًا عن نفسه، ثم لم يدخل فيهم، رجع عن قوله كلِّه أجمع، وهو قول أهل السنة.

=› «ጀህሚዩ አላህ በሁሉ ቦታ እንዳለና በአንድ ቦታ ሳይኖር በሌላ እንደማይሆን ሲሞግት በአላህ ላይ እየዋሸ መሆኑን ለማወቅ “አላህ ምንም ነገር ሳይኖር የነበረ አይደለምን?” በለው! እርሱም “ነበረ!” ይላል። “ነገሮችን በፈጠረ ጊዜ በራሱ ውስጥ ፈጠራቸው ወይስ ከራሱ ውጭ?” በለው። ያኔ ወደ ሶስት መልሶች ያመራል፤ ከነርሱ አንዱን ከመምረጥ ውጭ አማራጭ የለውም፦
1- አላህ ፍጡራንን በራሱ ውስጥ እንደፈጠራቸው ከሞገተ በርግጥ ይከፍራል፤ አጋንንትን፣ ሰይጣናትንና ኢብሊስን በውስጡ እንደፈጠረ ሞግቷልና!
2- “ከራሱ ውጭ ፈጥሯቸው ከዚያም በውስጣቸው ገብቷል!” ካለም ክህደት ነው፤ በአፀያፊ፣ በቆሻሻና በተልካሻ ቦታ ሁሉ እንደገባ ሞግቷልና!
3- “ከራሱ ውጭ ፈጥሯቸው ሲያበቃ በውስጣቸው አልገባም!” ካለ ደግሞ ከመጀመሪያው ንግግሩ መሉ በሙሉ ተመልሷል! ይኸኛውም የአህሉ’ስ-ሱና አቋም ነው!» [አሕመድ ኢብኑ ሐንበል - “አር-ረድ-ዱ ዐለ’ዝ-ዘናዲቀቲ ወ’ል-ጀህሚይ-ያህ” ገፅ 300-301]
ልብ ይበሉ! “አላህ አሁን ያለው ያኔ እንደነበረው ነው!” በሚለው ብንስማማ በላይኛው የኢማሙ ማብራሪያ መሰረት ከፍጥረተ አለሙ የቦታ ገደብ ውጭ መሆኑን አረጋገጥን ማለት ነው፤ አላህ ፍጡራኑን ያስገኘው ከራሱ ውጭ እንደሆነ ግልፅ ነውና! ከውጭ ከሆነ ደግሞ ከበላያቸው እንጂ ከበታች አይሆንም! እነዚያ ሙግተኞች ግን ከፍጥረተ አለሙ ውጭ መሆኑን ራሱ አይቀበሉም! የኢማሙ ጥያቄ እጅግ ቀላል ስሌት ሆኖ ሳለ የዘንድሮ ጀህሚያዎች የመረጡት የሽሽት መልስ ግን እንደ ሚስጥረ ስላሴ የተቋጠረ ነው! «በፍጥረተ አለሙ ውስጥ አይደለም፤ ከዚያ ውጭም አይደለም! ከላይም አይደለም፤ ከታችም አይደለም!..» ይሉናል።
- ለመሆኑ የአላህ ህልውና ህሊናዊ ብቻ ነው ወይስ እውን?
የቀድሞው የአሽዐሪይ-ያህ መንገድ እውነተኛ ጠንሳሽ የሆነው ኢብኑ ኩል-ላብ (243 ዓ.ሂ) እንኳ ያኔ እንዲህ ብሎ ነበር፦
وأَخْرَجُ من النظر والخبر قولُ من قال: لا هو في العالم ولا خارجٌ منه! فنفاه نفيًا مستويًا؛ لأنه لو قيل له: صفه بالعدم، ما قدر أن يقولَ فيه أكثرَ منه
«ከአእምሯዊ ምልከታም ከነጋሪት ማስረጃዎችም (ቁርኣንና ሐዲሥ) ይበልጥ ያፈነገጠው ደግሞ “በፍጥረተ-ዓለሙ ውስጥም አይደለም፤ ውጭም አይደለም!” በማለት (ሁለቱንም) እኩል የሚያፈርሰው ተናጋሪ ንግግር ነው! ምክንያቱም “(አላህን) ጭራሽ የማይገኝ በሆነ ኢምንትነት መገለጫ ግለፀው!” ቢባል ከዚህ የበለጠ ንግግር ሊናገር አይችልምና!»
[“በያኑ ተልቢሲ’ል-ጀህሚይ-ያህ” ጥራዝ 1ገፅ 44፣ “ደርኡ ተዓሩዲ’ል-ዐቅሊ ወን-ነቅል” ጥራዝ 6/119) (-ከኢብኑ ፉረክ እንዳተላለፉት)]
- አዎን! ይህ አፍራሽ ሀተታ «አላህ የለም!» ከሚለው መልዕክት የሚለይበትን ይዘት የሚያብራሩበት አንደበት የላቸውም! እንዲሁ ብቻ «አላሁ መውጁዱን ቢላ ከይፍ!» ማለትም፦ «አላህ ያለ ሁኔታ የሚገኝ ነው!» ወደሚል መፈክር ይጣደፋሉ! ያ የማይፈታ ትንግርታቸው የሚያሳድረውን አሉታዊ እንድምታ ለማለዘብ የመረጡት መሸሻ ይህ ነው። ይህን ንግግር አስመልክቶ ሶስት ነጥቦችን ለማንሳት እወዳለሁ፦
‪#‎አንደኛ፦ ማንኛውም ነገር የራሱ የሆነ ሁኔታ ሳይኖረው ገሀዳዊ ግኝት ሊኖረው አይችልም፤ ሊታሰብ ይችል ይሆናል፤ እውን ግን አይሆንም!
ለዚህም ነው ከጥንት ጀምሮ የኢስላም ሊቃውንት ስለ አላህና መገለጫዎቹ ሁኔታ “እንዴት” (ከይፍ) እያሉ መጠየቅን ያወገዙት ስለ ጉዳዩ ስላልተነገረንና አእምሯችንም ስለማይደርስበት እንጂ “አላህ ያለ ሁኔታ ያለ ነው!” በሚል መነሻ አይደለም!ለምሳሌ አል-ኢማም ዐብዱ’ል-ዐዚዝ አል-ማጀሹን (164 ዓ.ሂ) የአላህን ባህሪያት ስለሚያስተባብሉት ጀህሚያዎች በሰጡት ምላሽ ላይ የተናገሩትን እንደምሳሌ እንይ፦
وَإِنَّمَا يُقَالُ: كَيْفَ كَانَ؟، لِمَنْ لَمْ يَكُنْ مَرَّةً ثُمَّ كَانَ، فَأَمَّا الَّذِي لَا يَحُولُ، وَلَا يَزُولُ، وَلَمْ يَزَلْ، وَلَيْسَ لَهُ مِثْلٌ، فَإِنَّهُ لَا يَعْلَمُ كَيْفَ هُوَ إِلَّا هُوَ
=› « “እንዴት ሆነ?” የሚባለው እኮ አንድ ጊዜ ያልነበረ ሆኖ ከዚያ ስለሆነ ነገር ነው! ጭራሽ የማይለወጠው፣ የማይወገደው፣ ሁሌም የነበረውና አምሳያ የሌለው ግን እርሱ እንዴት እንዳለ ከርሱ በቀር የሚያውቅ የለም!»
[ኢብኑ በጥ-ጠህ - “አል-ኢባነህ” (ሶስተኛው ክፍል) ጥራዝ 3 ገፅ 64፣ አዝ-ዘሀቢይ “አል-ዑሉዉ ሊል-ዐሊይ-ዪ’ል-ገፍ-ፋር” ገፅ 141 ቁጥር 386]
- “አላህ ሁኔታ የለውም” ሳይሆን “እንዴት እንዳለ ከርሱ በቀር የሚያውቅ የለም!” ማለታቸው ይሰመርበት።
‪#‎ሁለተኛ፦ በቁርኣንና በሐዲሥ የተረጋገጡ የጌታ ባህሪያትን በጥቅሉ ማፅደቅ ሁኔታቸውን ከመግለፅ አይመደብም፤ ያ ሌላ ይሄ ሌላ! ያስተውሉ! ስለባህሪያቱ ዝርዝር ይዘትና ሁኔታ መናገርን ያወገዙት የአበው ሊቃውንት ራሳቸው እነዚያን ባህሪያት ያፀድቁ እንደነበር፤ ብሎም የማያፀድቁትን ሁሉ አጥብቀው ይኮንኑ እንደነበር የጥንቶቹ መዛግብት በሙሉ ይመሰክራሉ!
‪#‎ሶስተኛ፦ አል-ኢማም ኢብኑ ዐብዲ’ል-በር (463 ዓ.ሂ) ለመሰል ውዥንብር መልስ ሲሰጡ እንዲህ ይላሉ፦
فإِنْ قَالَ: إِنَّهُ لَا يَكُونُ مُسْتَوِيًا عَلَى مَكَانٍ إِلَّا مَقْرُونًا بِالتَّكْيِيفِ، قِيلَ: قَدْ يَكُونُ الِاسْتِوَاءُ وَاجِبًا وَالتَّكْيِيفُ مُرْتَفِعٌ، وَلَيْسَ رَفْعُ التَّكْيِيفِ يُوجِبُ رَفْعَ الِاسْتِوَاءِ، وَلَوْ لَزِمَ هَذَا لَزِمَ التَّكْيِيفُ فِي الْأَزَلِ؛ لِأَنَّهُ لَا يَكُونُ كَائِنٌ فِي لَا مَكَانٍ إِلَّا مَقْرُونًا بِالتَّكْيِيفِ، وَقَدْ عَقلْنَا وَأَدْرَكْنَا بِحَوَاسِّنَا أَنَّ لَنَا أَرْوَاحًا فِي أَبْدَانِنَا وَلَا نَعْلَمُ كَيْفِيَّةَ ذَلِكَ، وَلَيْسَ جَهْلُنَا بِكَيْفِيَّةِ الْأَرْوَاحِ يُوجِبُ أَنْ لَيْسَ لَنَا أَرْوَاحٌ! وَكَذَلِكَ لَيْسَ جَهْلُنَا بِكَيْفِيَّة "عَلَى عَرْشِهِ" يُوجِبُ أَنَّهُ لَيْسَ عَلَى عَرْشِهِ
=› «“(አላህ) ሁኔታው አብሮ ሳይገለፅ በ‘ቦታ’ ላይ መሆን አይችልም!” ካለ እንዲህ ይባላል፦
“ስለሁኔታው ጭራሽ የማይወሳ ሆኖ እያለ ‘ኢስቲዋእ’ (በዐርሹ ላይ መሆኑ) የፀና ይሆናል! ስለሁኔታው አለመወሳቱ የ‘ኢስቲዋእ’ መሻርን አያስከትልም! ይህ የግድ ቢሆን ኖሮ ዝንተ አለሙን (ፍጡራን ገና ሳይኖሩ በፊት) ስለ ነበረበት ሁኔታ ማውሳትን ያስከትል ነበር! ምክንያቱም ማንኛውም ነገር ሁኔታ ሳይኖረው ያለ ቦታም ሊኖር አይችልምና! መቼም በሰውነታችን ሩሕ (ነፍስ) እንዳለን ተገንዝበናል፤ በህዋሳችንም ደርሰንበታል! ስለ ሁኔታዋ ግን አናውቅም! ስለ ሩሓችን ሁኔታ አለማወቃችን ግን ሩሕ እንደሌለን አያመለክትም! ልክ እንዲሁ (አላህ) በዐርሹ ላይ የሆነበትን ሁኔታ አለማወቃችን በዐርሹ ላይ አለመሆኑን አያመለክትም!”»
[ኢብኑ ዐብዲ’ል-በር - “አት-ተምሂድ” ጥራዝ 7 ገፅ 137]

PART 4 አንድ ጥያቄና አስር መልሶቹ!

    አንድ ጥያቄና አስር መልሶቹ!

ሁለተኛው መንገድ (የሙግቱ አሰካክ ላይ ያነጣጠረ ዝርዝር ምላሽ)
«“አላህ በዐርሹ ላይ ነው!” ካላችሁ ዐርሽን ከመፍጠሩ በፊት የት ነበር?!» «ዐርሽም ሆነ ሌላ ቦታ ሳይፈጠር የነበረ ጌታ ነው፤ እርሱ የማይቀያየር በመሆኑ ዛሬም እንደያኔው ያለ ቦታ ነው ያለው!»
የሚለውን የሙግት አሰካክ በታትነን እንመርምረው፦
(2-1) በቅድሚያ «“አላህ በዐርሹ ላይ ነው!” ካላችሁ ዐርሽን ከመፍጠሩ በፊት የት ነበር?!» የሚለው ቃና ራሱ ስህተት ነው፤ ምክንያቱም “የት” የሚለው ጥያቄ መልስ የሚያገኘው ለገለፃ የሚያግዝ መነሻ (reference) ሲኖር ነው! ለዚህም ነው “አላህ የት ነው?” ሲባል፦ “ከዐርሹ በላይ፣ ከፍጥረተ-ዓለሙ ውጭ፤.. ወዘተ” የምንለው። በዚህ ገለፃ ላይ ዐርሽን ወይም አጠቃላይ ፍጥረተ አለሙን እንደ መነሻ በማጣቀስ የአላህ የበላይነትን አውስተናል። ሆኖም ዐርሽም ሆነ ሌላ ፍጡር ጭራሽ ባልነበረበት ሁኔታ አላህ የት እንደነበር በምን ቋንቋ መመለስ ይቻላል? ከምንስ በላይ ነበር ይባላል?
ልብ ይበሉ! የህልውናው የበላይነት (ዑሉው) ከማንነቱ የማይነጠል የዝንተ አለም መገለጫው ነው! ዐርሹን ከፈጠረ በኋላ በርሱ ላይ መሆኑ (ኢስቲዋእ) ደግሞ ይህንን የሚያጎላ አድራጎታዊ መገለጫ ነው።
- ደግሞም ከላይ እንደተብራራው የማናውቀው እውነታ የምናውቀውን አይሽርም!
(2-2) «አላህ ዐርሽም ሆነ ሌላ ቦታ ሳይፈጠር የነበረ ጌታ ነው!..» የሚለውን መነሻ ከመልዕክት አንፃር ስንፈትሸው ደግሞ፦
- ይህ በመሰረቱ የውዝግብ ርዕስ አይደለም፤ ሆኖም አላህ ከዐርሹ በላይ ከመሆኑ እውነታ ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚጋጭ ባለመሆኑ በዚህ ሂደት መጠቀሱ ምንም አይፈይድም!
ይህን ይበልጥ የሚያብራራው ደግሞ ቀጣዩ ነጥብ ነው፦
(2-3) «እርሱ የማይቀያየር ጌታ ስለሆነ..» የሚለውን ገለፃ በተመለከተ ደግሞ ጥቂት ነጥቦችን አብረን እንቃኝ፦
‪#‎ሀ- በቁርኣንና በሐዲሥ የተረጋገጡትን የጌታ ባህሪያት በሚያጠራጥር ወይም በሚያሳቅቅ ቃል መግለፅ እውነታውን አይቀይረውም፤ ልብ ይበሉ!

 አል-ኢማም አሕመድ (241 ዓ.ሂ) እንዲህ ብለው ነበር፦
..وَلَا نُزِيلُ عَنْهُ صِفَةً مِنْ صِفَاتِهِ لشَنَاعَةٍ شُنِّعَتْ..
=› «የሚፀየፍ ተፀይፎ ስላወገዘ (ብለን) ከባህሪያቱ አንዱንም አናስወግድም!»
[ኢብኑ በጥ-ጠህ - “አል-ኢባና” ጥራዝ 3 ገፅ 326፣ ኢብኑ ቁዳማህ - “ዘም-ሙ’ት-ተእዊል” ገፅ 22]
‪#‎ለ- “መቀየር” ፣ “መለወጥ” እና መሰል ቃላት በዚህ ሂደት የሚፈለግባቸው ፍልስፍናዊ ይዘታቸው እንጂ ቋንቋዊው መልዕክታቸው አለመሆኑን ማወቅ የግድ ይለናል። በዚህም መሰረት የላይኛው ሙግት ባለቤቶች የአላህን ከዐርሹ በላይ መሆን ብቻ ሳይሆን እርሱ በሚሻ ጊዜ የሚፈፅማቸውን አድራጎታዊ መገለጫዎች በሙሉ በ“መቀየር” እና በ“ክስተት” ስም ውድቅ ያደርጋሉ!
ለምሳሌ፦ በፈለገው ጊዜ መናገሩን “‘ክስተት’ ነው!” በማለት ያጣጥሉታል፤ በቁርኣኑ እንዳፀደቀው በእለተ-ቂያማህ ለፍርድ መምጣቱን “እንቅስቃሴ ነው..!” ሲሉ ያስተባብሉታል። ምክንያቱን ሲያብራሩ ደግሞ «መንቀሳቀስም ሆነ አለመንቀሳቀስ ሁለቱም ክስተት ናቸው! ክስተት ደግሞ መቀየር ነው! ፈጣሪ ደግሞ አይቀየርም!..» ይላሉ።
- በመሰረቱ እኛ በቁርኣንና በሐዲሥ የሌሉ አሻሚ ገለፃዎችን በአዎንታዊም ይሁን በአፍራሽ መልኩ አንጠቀምም! በቃ! በእምነታችን ላይ የቁርኣንና የሐዲሥ ገለፃን አንተላለፍም! እንደ “ክስተት” እና “መቀየር” ያሉ ቃላት እውነታን በሚጥስ መልኩ ለሚታለመው ውጤት እንዲውሉ የሚቆለመሙና ከቋንቋዊ ይዘታቸው የወጡ መልዕክቶች የሚታጨቁባቸው አሻሚ ገለፃዎች ናቸውና!
- በዚህ ላይ ደግሞ መናገርም ይሁን መንቀሳቀስና አለመንቀሳቀስ “መቀየር” መሆናቸው የነሱ ፍልስፍናዊ አጠራር እንጂ ሌሎች ባለ አእምሮዎች የሚስማሙበት እንዳልሆነ ግልፅ ነው!
- እንደሚታወቀው በየትኛውም ቋንቋ አንድ ነገር “ተቀየረ” የሚባለው ከቀድሞው ይዘቱ የተለየ አዲስ መገለጫ ሲኖረው ነው።
ለምሳሌ፦ አንድ ሰው በበሽታ ምክንያት ሲከሳ ወይም ሲጠቁር ፣ ወይም አርጅቶ ፀጉሩ ሲሸብት አሊያም በምቾት ሲወፍር ወይም ሲቀላ “ተቀየረ” ይባላል። ስነ ምግባሩ ሲሻሻል ወይም ሲበላሽም “ተቀየረ” ይባላል።
የአየሩ ሙቀት ከተለመደው በላይ ከፍ ወይም ዝቅ ሲል እንዲሁም ምግብ ሲሻግት ወይም ጠረኑ ሲለወጥ አሊያም የመጠጥ ቀለም ይዘቱን ሲለቅ እንደዚሁ “ተቀየረ” ይባላል። ወዘተ...
በአንፃሩ ደግሞ አንድ ሰው መናገር ሲጀምር ወይም ተናግሮ ዝም ሲል፣ ወይም ሲቆም አሊያም ሲቀመጥ፣ በጥቅሉ ሲንቀሳቀስና እስቅስቃሴውን ሲተው ከልማዱ እስካልወጣ ድረስ “ተቀየረ” አይባልም። በጥቅሉ አንድን ድርጊት ስለፈፀመ ብቻ ድርጊቱ እንደ “መቀየር” አይታሰብም፤ በዚህ ቃልም አይገለፅም!
[ለተጨማሪ ማብራሪያ “ደርኡ ተዓሩዲ’ል-ዐቅሊ ወን-ነቅል” ጥራዝ 4 ገፅ 72-75 እንዲሁም “መጅሙዑ’ል-ፈታዋ” ቅፅ 6 ገፅ 249-250 ይመልከቱ።]
በዚህ መሰረት “አላህ አይቀያየርም!” ሲባል የህልውናው የበላይነት መቼም የማይለወጥ፣ የባህሪያቱ ምጥቀት መቼም የማይከስም፣ ዘልአለማዊነቱ የማይቋረጥ፣ እንደፍጡራን የጉድለት ክስተቶችን የማያስተናግድ ፍፁም መሆኑን ለማሳየት ከሆነ ትክክለኛ መልዕክት ይሆናል።
እነዚያ ሙግተኞች ይህን የሚሉት ግን ይህን ጉልህ መልዕክት ወጥነው አይደለም! አዎን! “ፈጣሪ አይቀያየርም!” ሲሉ የሰማ የዋህ ለጌትነቱ ከማይገቡ ጉድለቶችና ጠንቆች እያላቁት ይመስለው ይሆናል! እውነታው ግን የ“መቀየር”ን የታወቀ መልዕክት በመቀየር አላህ ስለራሱ ያፀደቃቸውን እውነታዎች እየቀየሩ፣ አድራጊነቱንም እየገደቡ መሆናቸው ነው! አዎን! በአሻሚ ገለፃዎች ተከልለው በቁርኣን የተረጋገጡ መገለጫዎቹን ይንዳሉ!
ሙስሊሞች እንደ ንግግር፣ መፍጠር፣ ለፍርዱ መምጣት፣ ከዐርሹ ላይ መሆን ያሉ መሰል አድራጎታዊ የጌታ መገለጫዎችን እንደ መቀየር እንደማያስቡ ግልፅ ነው።
የፍጡር አድራጎት እንኳ መቀየር ካልሆነ የአላህ አድራጎት ሁኔታ ጭራሽ በአእምሮ የማይደረስበትና ከፍጡራን ሁኔታ እጅግ የተለየና የላቀ መሆኑ እየታወቀ እንዴት በ“መቀየር” ይገለፃል?!
እንደሚታወቀው ፍጥረታት ከመፈጠራቸው በፊትና ከተፈጠሩ በኋላ ያለው ልዩነት በቀጥታ የሚመለከተው ፈጣሪን ሳይሆን ፍጡራንን ራሳቸውን ነው! የፍጡራን ህልውና ካለመኖር ወደ መኖር በመሸጋገሩ የአዲስነት ክስተትን አስተናግዷል። አላህ ግን ሁሌም ፈጣሪ፣ ሁሌም የሻውን አድራጊ ከመሆን አልተወገደም! ያኔ ብቻውን የነበረ መሆኑ፣ አሁን ደግሞ ፍጡራን በመኖራቸው ከነርሱ በላይ መሆኑ የማንነት ለውጥ ነውን?
ከላይ እንዳየነው የህልውናው የበላይነት (ዑሉው) ከማንነቱ የማይነጠል የዝንተ አለም መገለጫው ነው! ዐርሹን ከፈጠረ በኋላ በርሱ ላይ መሆኑ (ኢስቲዋእ) ደግሞ ይህንን የሚያጎላ አድራጎታዊ መገለጫ እንጂ መቀየር አይደለም!
ስለሆነም የአላህ ከዐርሹ በላይ መሆን ከመቀየር ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የሚዛመድበት መንገድ የለምና በባዶ ማስፈራሪያ ፅኑ መለኮታዊ እውነታን መፃረር አይቻልም!
ደግሞም፦
‪#‎ሐ- አላህ የሻውን ሁሉ ማድረጉ የምሉእነቱ መገለጫ እንጂ ጉድለት ሊሆን አይችልም! እንዲያውም አድራጊ የሆኑ ነገሮች አድራጊ ባልሆኑት ላይ መሰረታዊ ብልጫ እንዳላቸው የማንም አእምሮ አይክድም! ስለሆነም ይህንን ፅኑ እውነታ በአሻሚ ቃላት መናድ አይቻልም!
ታዋቂው የኢስላም ሊቅ አል-ፉደይል ኢብኑ ዒያድ (187 ዓ.ሂ) እንዲህ ይላሉ፦
«إِذَا قَالَ لَكَ جَهْمِيٌّ: أَنَا أَكْفُرُ بِرَبٍّ يَزُولُ عَنْ مَكَانِهِ، فَقُلْ: أَنَا أُؤْمِنُ بِرَبٍّ يَفْعَلُ مَا يَشَاءُ»
«አንድ ጀህሚይ “እኔ ከቦታው በሚወገድ ጌታ እክዳለሁ!” ካለህ “እኔ ደግሞ የሻውን በሚሰራ ጌታ አምናለሁ!” በል!»
[አል-ቡኻሪይ - “ኸልቁ አፍዓሊ’ል-ዒባድ” ጥራዝ 2 ገፅ 36 ቁጥር 61፣ ኢብኑ በጥ-ጠህ - “አል-ኢባናህ” (ሶስተኛው ክፍል) ጥራዝ 3 ገፅ 204፣ አል-ላለካኢይ - “ሸርሑ ኡሱሊ’ዕቲቃዲ አህሊ’ስ-ሱን-ናህ” ጥራዝ 2 ቅፅ 3 ገፅ 452]
እንዲሁም አል-ኢማም ኢስሓቅ ኢብኑ ራሀወይህ (238 ዓ.ሂ) እና አል-ኢማም የሕያ ኢብኑ መዒን (233 ዓ.ሂ) ተመሳሳይ ንግግር አስፍረዋል።
[ኢብኑ በጥ-ጠህ - “አል-ኢባናህ” (ሶስተኛው ክፍል) ጥራዝ 3 ገፅ 206፣ አል-ላለካኢይ - “ሸርሑ ኡሱሊ’ዕቲቃዲ አህሊ’ስ-ሱን-ናህ” ጥራዝ 2 ቅፅ 3 ገፅ 453፣ አል-በይሀቂይ - “አል-አስማኡ ወ’ስ-ሲፋት” ጥራዝ 2 ገፅ 375-376፣ አዝ-ዘሀቢይ - “ሲየሩ አዕላሚ’ን-ኑበላእ” ጥራዝ 11 ገፅ 376]
ስለዚህ በመሰል ስልቶች ቁርኣናዊ እውነታን መጋፋት መረጃዎችን ከማጣመም በቀር የሚፈይደው ትርፍ የለም!